
ETHIOPIANREPORTER.COM – የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች በሜዲካል ቱሪዝም ዘርፍ ከኢትዮጵያ ጋር መሥራት እንደምትፈልግ አስታወቀች
የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ከኢትዮጵያ ጋር በሕክምናው ዘርፍ የልምድ ልውውጥ በማድረግ፣ ቴክኖሎጂን በማስተዋወቅ፣ በሌሎች አገሮች ውድ የሚባሉ ሕክምናዎችን በተመጣጣኝ ዋጋ በመስጠትና በአጠቃላይ በሜዲካል ቱሪዝም ዘርፍ ከኢትዮጵያ ጋር መሥራት እንደምትፈልግ የዱባይ የኢኮኖሚና ቱሪዝም ዲፓርትመንት (ዲኢቲ) አስታውቋል፡፡
ከሚያዝያ 23 እስከ 26 ቀን 2015 ዓ.ም. ድረስ በዱባይ ለ30ኛ ጊዜ የተካሄደውን የዓረቢያን ትራቭል ማርኬት አስመልክቶ፣ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከተለያዩ የአፍሪካ አገሮች ለመጡ ጋዜጠኞች ቃለ መጠይቅ የሰጡት የዱባይ ኢኮኖሚና ቱሪዝም ዲፓርትመንት ዓለም አቀፍ ኦፕሬሽን ተባባሪ ምክትል ፕሬዚዳንት ሚስ ሆር አልካጃ እንዳሉት፣ ዱባይ በዓለም በሕክምናው ዘርፍ በቴክኖሎጂ ከበለፀጉና በተለይም ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ዘመናዊ ሕክምና ከሚሰጡ ቀዳሚ አገሮች የምትመደብ ናት፡፡ ይህንን ልምዷን ለኢትዮጵያ ማካፈልና በሜዲካል ቱሪዝም ዘርፍ በኢትዮጵያ የማይገኙ የሕክምና አገልግሎቶችን ለመስጠትም እየሠራች ትገኛለች፡፡
በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ሕክምና በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ወደሚታገዝበት ደረጃ እየተሸጋገረ መሆኑን፣ ይህም ሕሙማንን በተመጣጣኝና ከሌሎች አገሮች ሲነፃፀር ዝቅተኛ በሚባል ወጪ ጥራቱን የጠበቀና ፍቱን ሕክምና ለመስጠት እንደሚያስችል አክለዋል፡፡
እንደ ሚስ ሆር፣ አገራቸው በሕክምና ባለሙያ፣ በዘመናዊ መሣሪያ፣ በመድኃኒትና በሕክምና ግብዓት የተሟሉ የሕክምና ተቋማት ያሏት ሲሆን፣ የሕክምና ወጪ ሙሉ ለሙሉ ከፍለው መታከም ለማይችሉ አስተያየት የሚደረግበት አሠራርም አለ፡፡
Read More @ ethiopianreporter.com