
ADDISMALEDA.COM – የሳምንት ቆይታ በኤምሬቷ ወርቅ ከተማ – ዱባይ
በውበቷ ብዙዎች የሚማልሉላት ከተማ ናት፤ ዱባይ። በንግድ ሥራ ውስጥ የሚገኙ በርካቶችም እንደ ጓዳቸው ሄድ መለስ እያሉ ለሽያጭ የሚያቀርቧቸውን እቃዎች ይሸምቱባታል። የገንዘብ አቅም ያላቸው ሆነው ለመዝናናትና እረፍት ለማድረግ የሚመርጧትም ጥቂት አይደሉም። የአዲስ ማለዳው ታምራት አስታጥቄ ወደዚህች ከተማ አቅንቶ ነበር። በቆይታው የታዘበውንም እንደሚከተለው አጋርቷል።
መንደርደሪያ
የግማሽ ክፍለ ዘመን ዕድሜ ብቻ ያስቆጠረችውና በመካከለኛው ምሥራቅ የአረብ (ፐርሺያ) ባህረ ሰላጤን ታክካ የምትገኘው የተባበሩት አረብ ኤምሬት 83 ሺሕ 600 ሜትር ስኩየር የቆዳ ስፋት አላት። በያዝነው የፈረንጆች ዓመትም የሕዝብ ቁጥሯ 10.08 ሚሊዮን እንደደረሰ ተገምቷል። የኤምሬትን የቆዳ ስፋት ትንሽነት ከኢትዮጵያ አንጻር ለማስቀመጥ አፋር ክልል ያለው የቆዳ ይዞታ ላይ 10 ሺሕ ሜትር ስኩየር መጨመር ብቻ ይበቃል። ይሁንና እያስመዘገበች በምትገኘው ፈጣን የምጣኔ ሀብት ዕድገት ምክንያት ‹‹የባህረ ሰላጤው ነብር›› የሚል ቅጽል ሥም ወጥቶላታል።
የተባበሩት አረብ ኤምሬት እንደ ጎርጎሮሳውያን ዘመን አቆጣጠር በታኅሣሥ 2 ቀን 1971 በስድስት ኤምሬቶች ማለትም አቡ ዳቢ፣ ዱባይ፣ ሻርጃህ፣ አጅማን፣ ኡም አል ቁሚን እና ፉጃኤርህ በፌዴሬሽን መልክ የተመሠረተች ናት። ከኹለት ወራት በኋላም ራስ አል ኬኢማህ ስድስቱን በመቀላቀል የፌዴሬሽኑ ሰባተኛ አካል ሆኗል።
Read More @ addismaleda.com